የካንሰር ህመም በተለያዩ ምክንያቶች በዘረመሎች ላይ በሚደርሱ ጉዳቶች ይከሰታል። ስለዚህ ከዚህ በታች የተዘረዘሩት ምክንያቶች በተለያየ መልኩ የሴል ሳይክልን የሚቆጣጠሩ የፍተሻ ዘረ መሎች (genetic check points) ወይም ካንሰር እንዳያድግ የሚያደርጉ ዘረመሎች (tumor suppressor genes) ላይ ጉዳት በማድረስ ለካንሰር ህመም የሚዳርጉ ናቸው፡፡ እነዚህን ምክንያቶች ማወቁ ደግሞ ካንሰርን ለመከላከል የመጀመሪያው እርምጃ ነው፡፡ ለመገንዘብ እንደሚቻለውም ከ90-95% የሚሆኑት የካንሰር አጋላጭ ምክንያቶች ሰው ሰራሽ፤ መጥፎ በሆነ የአኗኗር ዘይቤ በመከተል የሚከሰቱ ሲሆኑ ቀሪወቹ 5-10% ምክንያቶች ደግሞ በዘር የሚተላለፉ ናቸው፡፡
የሚከተሉት ግን ለካንሰር የመጋለጥ እድላችንን የሚጨምሩ ናቸዉ።
1. እድሜ – ካንሰር ማንኛውንም የእድሜ ክልል ቢያጠቃም፡ በየእድሜ ክልሉ በብዛት የሚከሰቱ ግን አሉ፡፡ ለምሳሌ የደም ካንሰር በህጻናት፡ የጡት ካንሰር ደግሞ እድሜ ሲጨምር የሚከሰቱ ናቸው፡፡
2. ጾታ – የጡት ካንሰር በወንዶች ላይ ከሚከሰተው ይልቅ በሴቶች ላይ 150-200 እጥፍ ያህል ጨምሮ ይታያል፡፡
3. ትንባሆ ማጨስ (በተለያየ መልኩ – ሲጋራ፤ ሺሻ፤ በአፍንጫ የሚደረግ፤ የሚላመጥ)፡፡ ማጨስ የሚጎዳው አጫሹን ብቻ ሳይሆን በአካባቢው ያሉትንም ጭምር ነው፡፡
4. አልኮል መጠጥ – ለካንሰር ብቻ ሳይሆን ለልብና ተያያዥ ችግሮች ያጋልጣል፡፡ በቅርብ ጊዜ የወጡ ምርምሮች እንደሚሳዩትም ጤናማ ሊባል የሚችለው የአልኮል መጠን ዜሮ መሆኑን ነው (ማለትም ጭራሽ አለመጠጣት) ፡፡
5. ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ – ስብ፤ጨው፤ስኳር፤ሳቹሬትድ እና ትራንስ ፋት የበዛበት እንዲሁም በተቀራኒው አትክልትና ፍራፍሬን አዘውትሮ አለመጠቀም ነው፡፡ እንደ አሜሪካ ካንሰር ሶሳይቲ መረጃ መሰረት በቀን ውስጥ፡ 5 እና ከዚያ በላይ የአትክልትና ፍራፍሬዎችን፤ ከተዘጋጁና እሽግ ምግቦች ይልቅ ከጥራጥሬ የሚዘጋጁትን መጠቀም፤ የስጋ መጠንን በተለይም ቀይ፡የተዘጋጁና ብዙ ጮማ ያላቸውን በጣም መቀነስ እንዳለብን ይመከራል፡፡
6. ውፍረት – መረጃዎች እንደሚሳዩት ውፍረት 14% በወንዶች እንዲሁም 20% በካንሰር ለሚከሰተው ሞት ምክያት ነው፡፡
7. በቂ የአካል እንቅስቃሴ አለማድረግ– 5% ለሚሆኑ በካንሰር ለሚከሰት ሞት ምክያት ነው፡፡
8. ለአካባቢና አንዳንድ ስራ ቦታዎች ብክለት (ተገቢው ጥንቃቄ ክልተደረገ) መጋለጥ – ምሳሌ፤ የነዳጅ ማውጫዎች፤ቤንዚን፤አስቤስቶስ፤የቤት ውስጥ ጭስ
9. ኢንፌከሽን (በአይን የማታይታዩ በሽታ አምጭ ህዋሳት): ጥቂቶቹም
HPV (ሂዩማን ፓፒሎማ ቫይረስ) 99% ለሚሆነው የማህጸን በር ካንሰር ምክንያት ነው፡፡
ሄፓቲትስ ቢ እና ሲ (HCB እና) HCV – የጉበት ካንሰር፣ HIV
10. የጸሀይ ብርሀን – ለረጅም ሰአታት በቀን፤ ለረጅም አመታት፤ እንዲሁም የቆደ ቀለማቸው ስስ በሆኑ ሰዎች ላይ የቆዳ ካንሰር ያስከትላል፡፡አመሰግናለሁ፡፡
ዶ/ር አብዱ አደም
የካንሰር ህክምና ስፔሺያሊስትና ረዳት ፕሮፌሰር